ህዳር 15፣2016 - አዋሽ ባንክ በ2015 የበጀት ዓመት ከግብር በፊት 9.8 ቢሊዮን ብር ማትረፉን ተናገረ
- sheger1021fm
- Nov 25, 2023
- 1 min read
አዋሽ ባንክ በ2015 የበጀት ዓመት ከግብር በፊት 9.8 ቢሊዮን ብር ማትረፉን ተናገረ።
ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር 2.3 ቢሊዮን ብር ወይም የ31 በመቶ ዕድገት አሳይቷል ተብሏል።
አዋሽ ባንክ የባለአክስዮኖች 28ኛ ጠቅላላ ጉባዔ በዛሬው እለት አካሂዷል።

ባንኩ የ2015 በጀት ዓመትን በላቀ ስኬት ማጠናቀቁን አስረድቷል ።
የባንኩ ተቀማጭ በ2014 የበጀት ዓመት ከነበረበት የ23 በመቶ ወይም የ 35.4 ቢሊዮን ብር እድገት በማስመዝገብ 187.4 ቢሊዮን ብር ደርሷል ተብሏል።
ይህም በባንኩና በግል ባንኮች ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ መሆኑን ተረድቻለሁ ብሏል።
ባንኩ በበጀት ዓመቱ አንድ ቢሊዮን አራት መቶ ዘጠና ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ማስገባቱን፤ ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የሁለት መቶ ሀምሳ ሚሊዮን ዶላር ዕድገት አሳይቷል ተብሏል።
በሂሳብ ዓመቱ ውስጥ 224 ቢሊዮን ብር ብድር መስጠቱን የተናገረ ሲሆን ይህም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ40.9 ቢሊዮን ብር ብልጫ እንዳለው አስረድቷል።
የባንኩ የተከፈለ ካፒታል 14.6 ቢሊዮን ብር መድረሱን የተናገረው አዋሽ ባንክ ይህም ብሔራዊ ባንክ ነባር ባንኮች በ5 ዓመት ጊዜ ውስጥ ሊደርሱበት ይገባል ብሎ ካስቀመጠው የካፒታል መጠን የበለጠ መሆኑን አስረድቷል።
የባንኩን የተከፈለ ካፒታል 43 ቢሊዮን ብር እንዲሆን መወሰኑን ያስረዳው አዋሽ ባንክ ይህም በግል ባንኮች ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ ነው ብሏል።
አዋሽ ባንክ ዓመቱን በላቀ ስኬት ያጠናቀቀው በአለም አቀፍ ደረጃ የሩሲያ እና ዩክሬን ጦርነት፣ ቀደም ሲል የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ካስከተለው ተጽኖና የዓለም ኢኮኖሚ ሳያገግም፣ በሀገር ቤት የሰላም እጦት በቀጠለበት ሁኔታ ውስጥ ሆኖ እንዲሁም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የሚሄደው የዋጋ ንረት ውስጥ አልፎ መሆኑን የባንኩ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ጉሬ ኩምሳ አስረድተዋል ።
ስራ ከጀመረ 29 ዓመታት የሞላው አዋሽ ባንክ በአሁኑ ሰዓት ከ875 በላይ ቅርንጫፎች እና ከ20,000 በላይ ሰራተኞች አሉኝ ብሏል።
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ… https://bit.ly/33KMCqz
Comments