top of page

ሐምሌ 17፣ 2016 - ኢሰመኮ በጎፋ ዞን ገዜ ወረዳ የደረሰው የተፈጥሮ አደጋ ያስከተለውን ሞት እና ጉዳት የሚመጣጠን ድጋፍ እና በአፋጣኝ ሊቀርብ ይገባል ሲል አሳሰበ

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን(ኢሰመኮ) በጎፋ ዞን ገዜ ወረዳ የደረሰው አሳሳቢ የተፈጥሮ አደጋ ያስከተለውን ሞት እና ጉዳት የሚመጣጠን የምግብ እና መሠረታዊ የሰብአዊ ድጋፍ በተቀናጀ እና በአፋጣኝ ሊቀርብ ይገባል ሲል አሳሰበ፡፡

 

ኢሰመኮ ባወጣው መግለጫ በዞኑ የደረሰውን ጉዳት የሚመጥን ምላሽ መስጠት ያስፈልጋል ሲል አስረድቷል፡፡

 

በጎፋ ዞን ሐምሌ 14 ቀን 2016 ዓ.ምረፋድ አራት ሰዓት ላይ በደረሰ የጎርፍ እና የመሬት ናዳ ምክንያት እስካሁን ከ229  በላይ ሰዎች መሞታቸው ተረጋግጧል፡፡

የሰብአዊ መብቶች መርሆችን እና ድንጋጌዎችን የሚያሟላ እንዲሆን ለማስቻል የሚመለከታቸው የፌዴራል መንግሥት አካላት እና ሀገራዊና ዓለም አቀፋዊ ድርጅቶች አፋጣኝ ርብርብ እንዲያደርጉ ኮሚሽኑ ጥሪ አቅርቧል፡፡

 

እስካሁን በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል እና በዞኑ የመንግሥት አካላት ትብብር፣ በሀገራዊ የሰብአዊ ድጋፍ አቅራቢ ድርጅቶች፣ እንዲሁም በአካባቢው ነዋሪዎች በወረዳው በድንገተኛ የናዳ አደጋ ጉዳት ለደረሰባቸው ሰዎች የተለያዩ ቁሳቁሶችን ጨምሮ የተወሰነ አፋጣኝ ድጋፍ መደረጉ አበረታች እንደሆነም ኢሰመኮ ጠቁሟል፡፡

የኢሰመኮ ተጠባባቂ ዋና ኮሚሽነር ራኬብ መሰለ የደረሰውን ከፍተኛ ጉዳት አሳሳቢነት በማስታወስ “በተፈጥሮ አደጋ ወቅት በተለይም በሴቶች፣ በሕፃናት፣ በአረጋውያን እና በአካል ጉዳተኞች ላይ የሚደርሰው ጉዳት የበለጠ ሊሆን እንደሚችል ከግንዛቤ ውስጥ እንዲገባ፣ በዚሁ ክስተት ሳቢያ ከመኖሪያ ቦታቸው ተፈናቅለው በጊዜያዊ መጠለያ የተጠለሉ ሰዎች አፋጣኝ ድጋፍ እንዲደረግላቸው” ጥሪ አቅርበዋል።

 

የአለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ቴዎድሮስ አድሃኖም ትናንት በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው በጎፋ ዞን በደረሰ አደጋ ማዘናቸው አስረድተው የድርጅቱ ቡድን አፋጣኝ የጤና አቅርቦት ድጋፍ ለማቅረብ ወደ ስፍራው አቅንቷል ብለዋል፡፡

 

በዞኑ ለደረሰው አደጋ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ እና ፕሬዘዳንት ሳህለ ወርቅ ዘውዴ የተሰማቸውን ሀዘን ገልጸዋል፡፡

Comments


bottom of page