ሐምሌ 23፣2016 - የባህር ማዶ ወሬዎች
- sheger1021fm
- Jul 30, 2024
- 1 min read
የፍልስጤማውያኑ የጦር ድርጅት(ሐማስ) በጋዛ የተኩስ አቁም ለማድረግ የሚካሄደውን ድርድር በማወላከፍ የእስራኤሉን ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታንያሁን ከሰሰ፡፡
ድርድሩ የሚካሄደው በአሜሪካ ተደግፎ በቀረበው የተኩስ አቁም ሀሳብ መሰረት እንደሆነ ሚድል ኢስት ሞኒተር ፅፏል፡፡
ሐማስ በእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር የቀረቡ ተጨማሪ ጥያቄዎች እና ቅድመ ሁኔታዎች ድርድሩን እያወላከፈው ነው ማለቱ ተሰምቷል፡፡
የፍልስጤማውያኑን የጦር እና የፖለቲካ ድርጅት (ሐማስ) የጋዛው ጦርነት እንዲቆም ይሻል፡፡
የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር በበኩላቸው ጦርነቱ የሚቆመው ሐማስ ሙሉ በሙሉ ሲደመሰስ ነው የሚል አቋም ይዘዋል፡፡
የእስራኤል የጋዛ የጦር ዘመቻ ከተጀመረ 10ኛ ወሩ ተቃርቧል፡፡

የእስራኤል የጦር ወቅት የደህንነት ካቢኔ በጎላን ኮረብታ ለተፈፀመው የቅዳሜ እለቱ የሮኬት ጥቃት አጣዳፊ የበቀል እርምጃ እንዲወሰድ ወሰነ፡፡
በቅዳሜ እለቱ የሮኬት ጥቃት 12 ሕፃናት እና አዳጊዎች መገደላቸው ቢቢሲ አስታውሷል፡፡
ለጥቃቱ እስራኤል ከሊባኖሱ ታጣቂ ቡድን (ሔዝቦላህ) ራስ አልወርድም ብላለች፡፡
አሜሪካም ጥቃቱ በሔዝቦላህ መፈፀሙን አረጋግጫለሁ ማለቷ ተጠቅሷል፡፡
ሔዝቦላህ ግን በቅዳሜው ጥቃት እጄ የለበትም ሲል አስተባብሏል፡፡
የጋዛው ጦርነት ከተቀሰቀሰ ወዲህ በእስራኤል ጦር እና በሔዝቦላህ መካከል ግዛት ተሻጋሪው ቁርቋሶ እየተባባሰ መምጣቱ ይነገራል፡፡
አሁን ያለው ውጥረት በሊባኖስ ወደሙሉ ጦርነት ሊሸጋገር ይችላል የሚል ስጋት አሳድሯል፡፡
ሔዝቦላህ የኢራን ሁነኛ የጦር እና የፖለቲካ ሸሪክ እንደሆነ መረጃው አስታውሷል፡፡
Comments