መስከረም 27፣2017 - የባህር ማዶ ወሬዎች
- sheger1021fm
- Oct 7, 2024
- 1 min read
የፈረንሳዩ ፕሬዘዳንት ኢማኑኤል ማክሮን በቃ ከእንግዲህ ለእስራኤል የጦር መሳሪያ አንሸጥም አሉ፡፡
ማክሮን ለእስራኤል የጦር መሳሪያ ማቅረባችንን እናቆማለን ያሉት እስራኤል የሊባኖስ ዘመቻቸዋን መክፈቷን ተከትሎ እንደሆነ አልጀዚራ ፅፏል፡፡
ፈረንሳይ የሊባኖሱ ጦርነት መላ ቀጠናውን ሊያደርስ ይችላል የሚል ስጋት እንደገባት ይነገራል፡፡
ኢማኑኤል ማክሮን አሁን ለመካከለኛው ምስራቅ የሚበጀው ከጦርነት ይልቅ ፖለቲካዊ መፍትሄ ፍለጋ ነው ማለታቸው ተሰምቷል፡፡
የፈረንሳዩ ፕሬዘዳንት አምና እስራኤል የጋዛ የጦር ዘመቻዋን እንደከፈተች ወደ አገሪቱ በመምጣቱ በቅድሚያ አይዞሽ ከጎንሽ ነን ካሉ የምዕራባዊያን አገሮች መሪዎች መካከል አንዱ ነበሩ፡፡
የጋዛው ጦርነት ከተጀመረ ዛሬ ዓመት ሞላው፡፡

የዩክሬይን ጦር በዳኔስክ ግዛት የሩሲያን የጦር ጄት መትቼ ጥያለሁ አለ፡፡
የሩሲያ የመከላከያ መስሪያ ቤት የጦር ጄቱ ተመትቶ ወድቋል ስለመባሉ ማረጋገጫም ይሁን ማስተባበያ እንዳልሰጠ አሶሼትድ ፕሬስ ፅፏል፡፡
በሌላ መረጃ የሩሲያ ጦር በዛው በዳኔስክ ግዛት ዜላኔ ድሩሔ የተባለውን ስፍራ ከዩክሬይን ጦር ቀምቻለሁ ማለቱ ተሰምቷል፡፡
ቀደም ብሎ የሩሲያ ጦር ቩሌዳር የተባለችውን ከተማ ከዩክሬይን ሰራዊት መቀማቱ ሲነገር ሰንብቷል፡፡
የቩሌዲር መቀማት የዩክሬይን ሰራዊት የጦር ቁመና እየተዳከመ መምጣቱን የሚጠቁም ነው ተብሏል፡፡
የዩክሬይ ጦርነት ከ2 ዓመት ከመንፈቅ በላይ ሆኖታል፡፡
በሩዋንዳ የማርበርግ በሽታ መከላከያ ክትባት መስጠት ተጀመረ፡፡
በሀገሪቱ የማርበርግ በሽታ በወረርሽኝ ደረጃ እየተዛመተ መምጣቱ ከተነገረ ከሳምንት በላይ እንደሆነው አልጀዚራ ፅፏል፡፡
በወረርሽኙ እስከ ትናንት የ12 ሰዎች ሕይወት ማለፉ ታውቋል፡፡
የወረርሽኙ መቀስቀስ ምክንያት ገና አልተደረሰበትም ተብሏል፡፡
በአጣዳፊ ግን መከላከያውን መክተብ እንደተጀመረ ተሰምቷል፡፡
ተጋላጭ የሆኑ የህክምና ባለሙያዎች እንዲሁም በበሽታው መያዛቸው ከተረጋገጠ ሰዎች ጋር ቅርበት የነበራቸው በቅድሚያ ከሚከተቡት መካከል ናቸው ተብሏል፡፡
ማርበርግ ኢቦላ መሰል ገዳይ በሽታ ነው፡፡
ከፍተኛ ደም መፍሰስ እና ትኩሳት አስከታይነቱ ከምልክቶቹ ከብዙው በጥቂቱ ናቸው ተብሏል፡፡
የኔነህ ከበደ
Comments