በኢትዮጵያ የፍላጎቱን ያህል አለም አቀፍ መስፈርቶችን ያሟሉ በቂ የሂሳብ ባለሞያዎች እንደሌሉ ተነገረ፡፡
የህዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው 4ኛ ዓመት የስራ ዘመን 19ኛ መደበኛ ስብሰባው የኢትዮጵያ የተመሰከረላቸው የሂሳብ ባለሙያዎች ኢንስቲትዩት ማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅ ላይ ተወያይቷል፡፡
ኢንስቲትዩቱ አለም አቀፍ መስፈርቶችን ያሟሉ ብቁ የሂሳብ ባለሙያዎችን በማሰልጠን የብቃት ማረጋገጫ የሚሰጥ ነው መባሉን ተከትሎ ስለ አስፈላጊነቱ ከምክር ቤት አባላት ጥያቄ ተነስቷል፡፡
የስልጠና ተቋም ከሆነ ኢንስቲትዩት በማቋቋም የመንግስትን ወጪ ከመጨመር ይልቅ ስራው ለምን በትምህርት ሚኒስቴር በኩል አልተሰራም የሚል ጥያቄ ከፓርላማ አባላት ተጠይቋል፡፡
የገንዘብ ሚኒስትር ዴኢታው ዶክተር እዮብ ተካልኝ ጥያቄ ያስነሳውን የተመሰከረላቸው የሂሳብ ባለሙያዎች ኢንስቲትዩት ማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅ አስመልክቶ በሰጡት ምላሽ፤ ኢንስቲትዩቱን ማቋቋም ያስፈለገው በሃገር ውስጥ ብቃት ያላቸው፤አለም አቀፍ መስፈርቶችን ያሟሉ በቂ የሂሳብ ባለሙያዎች ስለሌሉ ነው ብለዋል፡፡
በዚህም ምክንያት 500 የሂሳብ ባለሙያዎችን ወደ ልከን በውጭ ምንዛሪ በከፍተና ወጪ ለማስተማር ተገደናል የሚሉት ዶ/ር እዮብ በኢትዮጵያ እየሰሩ ያሉ የቢዝነስ አማካሪ ተቋማት እኛ ባለሙያ ስለሌለን ከጎረቤት ሃገራት አምጥተው እሰሩ ነው ብለዋል፡፡

እነዚህን አለም አቀፍ መስፈርቶችን የሚያሟሉ የሂሳብ ባለሙያዎችን ለማሰልጠን ራሱን የቻለ ኢንስቲትዩት ማቋቋም ያስፈለገበትን ምክንያትም አስረድተዋል፡፡
እንደ ዶክተር እዮብ ገለፃ በኢትዮጵያ በተለይ በግሉ ዘርፍ ኦዲተሮችና ባለሃብቶች በመደራደር ሁለትና ሶስት የውሸት ሪፖርቶች ይሰናዳሉ በዚህ መሃል ብዙ የሃገር ሃብት እየሸሸ ነው፡፡
በዚህ በሚቋቋመው ኢንስቲትዩት የሚፈሩት አለም አቀፍ ደረጃን ያሟሉ የሂሳብ ባለሙያዎች ስለሚሆኑ የውሸት ሪፖርቶችን ማስቀረት እንደሚቻልም አንስተዋል፡፡
የሚቋቋመው ተቋም በሂሳብ ባለሙያዎቹ አባልነት እንዲሁም በመንግስት ድጋፍ እንደሆነም የገንዘብ ሚኒስትር ዴኢታው ተናግረዋል፡፡
ተቋሙ የኢዲት ስራዎችን በአግባቡ የማሰራ ባለሙያን የመመቆጣጠርና የመቅጣት ሃላፊነት ተሰጥቶታል ተብሏል፡፡
በኢትዮጵያ አለም አቀፍ ደረጃን ያሟሉ 500 የሂሳብ ባለሙዎች ብቻ እንዳሉና ከእነዚህም የብቃት ማጋገጫ ያላቸው 250ው ብቻ መሆናቸውንም ሰምተናል፡፡
በምክር ቤቱ ውይይት ከተደረገበት በኋላ የኢትዮጵያ የተመሰከረላቸው የሂሳብ ባለሙያዎች ኢንስቲትዩትን ለማቋቋም የቀረበው ረቂቅ አዋጅ በሙሉ ድምፅ ፀድቋል፡፡
በድምፅ ያድምጡ…
ምንታምር ፀጋው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 YouTube: https://tinyurl.com/ky57kspd
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
📌 Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
📌 Linkedin : https://tinyurl.com/yhycs5r
Comments